Chap.   
የፍጥረት አጀማመር
☐ 1. በመጀመሪያ እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ሰማያትንና ምድርን ፈጠረ።
☐ 2. ምድርም ቅርጽ የለሽና ባዶ ነበረች።[1] የምድርን ጥልቅ ስፍራ ሁሉ ጨለማ ውጦት ነበር። የእግዚአብሔርም (ኤሎሂም) መንፈስ በውሆች ላይ ይረብብ ነበር።
☐ 3. ከዚያም እግዚአብሔር (ኤሎሂም) “ብርሃን ይሁን” አለ፤ ብርሃንም ሆነ።
☐ 4. እግዚአብሔርም (ኤሎሂም) ብርሃኑ መልካም እንደሆነ አየ፤ ብርሃኑን ከጨለማ ለየ።
☐ 5. እግዚአብሔርም (ኤሎሂም) ብርሃኑን “ቀን”፣ ጨለማውን “ሌሊት” ብሎ ጠራው። መሸ፤ ነጋም፤ የመጀመሪያ ቀን።
☐ 6. እግዚአብሔር (ኤሎሂም)፣ “ውሃን ከውሃ የሚለይ ጠፈር በውሆች መካከል ይሁን” አለ።
☐ 7. ስለዚህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ጠፈርን አድርጎ ከጠፈሩ በላይና ከጠፈሩ በታች ያለውን ውሃ ለየ፤ እንዳለውም ሆነ።
☐ 8. እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ጠፈርን “ሰማይ” ብሎ ጠራው። መሸ፤ ነጋም፤ ሁለተኛ ቀን።
☑ 9. ከዚያም እግዚአብሔር (ኤሎሂም)፣ “ከሰማይ በታች ያለው ውሃ በአንድ ስፍራ ይከማች፤ ደረቁ ምድር ይገለጥ” አለ፤ እንዳለውም ሆነ።
  መዝ 95:5  እርሱ ፈጥሮአታልና፣ ባሕር የእርሱ ናት፤ እጁም የብስን አበጀ።
  መዝ 24:1-2  የዳዊት መዝሙር ምድርና በእርሷ ያለው ሁሉ፣ ዓለምና በውስጧ የሚኖር ሁሉ የእግዚአብሔር ነው፤  እርሱ በባሕሮች ላይ መሥርቶአታልና፤ በውሆችም ላይ አጽንቶአታል።
  መዝ 33:7  የባሕርን ውሃ በአንድ ዕቃ ይሰበስባል፤[49] ቀላዩንም በአንድ ስፍራ ያከማቻል።
  2ጴጥ 3:5  ነገር ግን እነዚህ ሰዎች ሰማያት ከጥንት ጀምሮ በእግዚአብሔር ቃል ተፈጥረው እንደሚኖሩ፣ መሬትም በውሃ መካከልና በውሃም እንደ ተሠራች ሆን ብለው ይክዳሉ፤
  መክ 1:7  ወንዞች ሁሉ ወደ ባሕር ይፈሳሉ፤ ባሕሩ ግን ፈጽሞ አይሞላም፤ ወንዞች ወደ መጡበት ስፍራ፣ ወደዚያ እንደ ገና ይመለሳሉ።
  ምሳ 8:28-29  ደመናትን በላይ ባጸና ጊዜ፣ የውቅያኖስን ምንጮች በመሠረተ ጊዜ፣  ለባሕር ድንበርን በከለለ ጊዜ፣ ውሆችም የእርሱን ትእዛዝ እንዳያልፉ፣ የምድርንም መሠረቶች ወሰን ባበጀ ጊዜ፣
  ኢዮ 38:8-11  “ባሕር ከማሕፀን በወጣ ጊዜ፣ በር የዘጋበት ማን ነው?  ደመናውን ልብሱ፣ ጨለማንም መጠቅለያው አደረግሁለት፣  ድንበር ወሰንሁለት፤ መዝጊያና መወርወሪያውን አበጀሁለት።  ‘እስከዚህ ድረስ ትመጣለህ፤ ማለፍ ግን አትችልም፤ የዕቡይ ማዕበልህም ገደብ ይህ ነው’ አልሁት።
  መዝ 136:5-6  ሰማያትን በብልኀት የሠራ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና፤   ምድርን በውሃ ላይ የዘረጋ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና።
  ኤር 5:22  ልትፈሩኝ አይገባችሁምን?” ይላል እግዚአብሔር፤ “በእኔ ፊት ልትንቀጠቀጡስ አይገባምን? ለዘላለም ዐልፎት መሄድ እንዳይችል፣ አሸዋን ለባሕር ድንበር አደረግሁ፤ ማዕበሉ እየጋለበ ቢመጣ ከዚያ አያልፍም፤ ሞገዱ ቢጮኽም ሊያቋርጠው አይችልም።
  መዝ 104:3  የእልፍኝህን አግዳሚ በውሆች ላይ አኖርህ፤ ደመናትን ሠረገላህ አደረግህ፤ በነፋስ ክንፍ ትሄዳለህ።
  ኢዮ 26:10  ለብርሃንና ለጨለማ ድንበር ይሆን ዘንድ፣ በውሆች ላይ የአድማስ ክበብ አበጀ።
  መዝ 104:5-9  ለዘላለም እንዳትናወጥ፣ ምድርን በመሠረቷ ላይ አጸናሃት።  በጥልቁ እንደ ልብስ ሸፈንሃት፤ ውሆችም ከተራሮች በላይ ቆሙ።  በገሠጽሃቸው ጊዜ ግን ፈጥነው ሄዱ፤ የነጐድጓድህንም ድምፅ በሰሙ ጊዜ ሸሹ።  በተራሮች ላይ ፈሰሱ፤ ወዳዘጋጀህላቸው ስፍራ፣ ወደ ሸለቆዎች ወረዱ።  ተመልሰው ምድርን እንዳይሸፍኑ፣ አልፈውም እንዳይመጡ ድንበር አበጀህላቸው።
  ራእ 10:6  እርሱም ከዘላለም እስከ ዘላለም በሚኖረው፣ ሰማይንና በውስጡ ያሉትን፣ ምድርንና በውስጧ ያሉትን፣ ባሕርንና በውስጡ ያሉትን በፈጠረው በእርሱ ማለ፤ እንዲህም አለ፤ “ከእንግዲህ መዘግየት አይኖርም፤
  ዮና 1:9  እርሱም፣ “እኔ ዕብራዊ ነኝ፤ የብስንና ባሕርን የፈጠረውን፣ የሰማይን አምላክ እግዚአብሔርን አመልካለሁ” አለ።
  ኢዮ 26:7  የሰሜንን ሰማይ በሕዋው ላይ ዘረጋው፤ ምድርንም እንዲያው በባዶው ላይ አንጠለጠላት።
☐ 10. እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ደረቁን ምድር፣ “የብስ”፣ በአንድነት የተሰበሰበውን ውሃ፣ “ባሕር” ብሎ ጠራው። እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ይህ መልካም እንደሆነ አየ።
☐ 11. እግዚአብሔር (ኤሎሂም)፣ “ምድር ዕፀዋትንም፣ እንደየወገናቸው ዘር የሚሰጡ ተክሎችንና በምድር ላይ ዘር ያዘሉ ፍሬ የሚያፈሩ ዛፎችን እንደየወገናቸው ታብቅል” አለ፤ እንዳለውም ሆነ።
☐ 12. ምድር ዕፀዋትን፣ እንደየወገናቸው ዘር የሚሰጡ ተክሎችንና በውስጣቸው ዘር ያለባቸው ፍሬ የሚያፈሩትን ዛፎች በየወገኑ አበቀለች። እግዚአብሔርም (ኤሎሂም) ይህ መልካም እንደሆነ አየ።
☐ 13. መሸ፤ ነጋም፤ ሦስተኛ ቀን።
☐ 14. ከዚያም እግዚአብሔር (ኤሎሂም)፣ “ቀኑን ከሌሊት እንዲለዩ፣ የዓመት ወቅቶች፣ ቀናትና ዓመታት የሚጀምሩበትንም እንዲያመለክቱ፣
☐ 15. ለምድር ብርሃን የሚሰጡ ልዩ ልዩ ብርሃናት በሰማይ ይሁኑ” አለ፤ እንዳለውም ሆነ።
☐ 16. እግዚአብሔር (ኤሎሂም)፣ ለምድር ብርሃን ይሰጡ ዘንድ ሁለት ታላላቅ ብርሃናት አደረገ፤ ታላቁ ብርሃን በቀን እንዲሠለጥን፣ ታናሹ ብርሃን በሌሊት እንዲሠለጥን አደረገ። እንዲሁም ከዋክብትን አደረገ።
☐ 17. ለምድር ብርሃን እንዲሰጡ እነዚህን በሰማይ ጠፈር አኖራቸው።
☐ 18. ይኸውም በቀንና በሌሊት እንዲሠለጥኑ፣ ብርሃንን ከጨለማ እንዲለዩ ነው። እግዚአብሔርም (ኤሎሂም) ይህ መልካም እንደሆነ አየ።
☐ 19. መሸ፤ ነጋም፣ አራተኛ ቀን።
☐ 20. እግዚአብሔር (ኤሎሂም)፣ “ውሆች ሕይወት ባላቸው በሕያዋን ፍጡራን ይሞሉ፤ ወፎች ከምድር በላይ በሰማይ ጠፈር ይብረሩ” አለ።
☐ 21. በዚህ መሠረት፣ እግዚአብሔር (ኤሎሂም) በባሕር ውስጥ የሚኖሩ ታላላቅ ፍጡራንን፣ በውሃ ውስጥ የሚርመሰመሱ ሕይወት ያላቸውን ነገሮች ሁሉ እንደየወገናቸው እንዲሁም ክንፍ ያላቸውን ወፎች ሁሉ እንደየወገናቸው ፈጠረ፤ እግዚአብሔርም (ኤሎሂም) ይህ መልካም እንደሆነ አየ።
☐ 22. እግዚአብሔርም (ኤሎሂም)፣ “ብዙ ተባዙ፤ የባሕርንም ውሃ ሙሏት፤ ወፎችም በምድር ላይ ይብዙ” ብሎ ባረካቸው።
☐ 23. መሸ፤ ነጋም፤ አምስተኛ ቀን።
☐ 24. እግዚአብሔር (ኤሎሂም)፣ “ምድር ሕያዋን ፍጡራንን እንደየወገናቸው፣ ከብቶችን፣ በምድር ላይ የሚሳቡ ፍጡራንንና የዱር እንስሳትን እያንዳንዱን እንደ ወገኑ ታስገኝ” አለ፤ እንዳለውም ሆነ።
☐ 25. እግዚአብሔር (ኤሎሂም) የዱር እንስሳትን እንደየወገናቸው፣ ከብቶችን እንደየወገናቸው፣ እንዲሁም በምድር ላይ የሚሳቡ ፍጡራንን እንደየወገናቸው አደረገ። እግዚአብሔርም (ኤሎሂም) ይህ መልካም እንደሆነ አየ።
☐ 26. እግዚአብሔር (ኤሎሂም)፣ “ሰውን በመልካችን፣ በአምሳላችን እንሥራ፤ በባሕር ዓሦች፣ በሰማይ ወፎች፣ በከብቶች፣ በምድር[2] ሁሉ ላይ፣ እንዲሁም በምድር በሚሳቡ ፍጡራን ሁሉ ላይ ሥልጣን ይኑራቸው” አለ።
☐ 27. ስለዚህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ሰውን በራሱ መልክ ፈጠረው፤ በእግዚአብሔር (ኤሎሂም) መልክ ፈጠረው፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው።
☐ 28. እግዚአብሔርም (ኤሎሂም)፣ “ብዙ ተባዙ፤ ምድርን ሙሏት፤ ግዟትም፤ የባሕርን ዓሦች፣ የሰማይን ወፎች፣ እንዲሁም በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትን ሕያዋን ፍጡራንን ሁሉ ግዟቸው” ብሎ ባረካቸው።
☐ 29. እግዚአብሔርም (ኤሎሂም)፣ እንዲህ አለ፤ “በምድር ላይ ያሉትን ዘር የሚሰጡ ተክሎችን ሁሉ፣ በፍሬያቸው ውስጥ ዘር ያለባቸውን ዛፎች ሁሉ ምግብ ይሆኑላችሁ ዘንድ ሰጥቻችኋለሁ።
☐ 30. እንዲሁም ለምድር አራዊት ሁሉ፣ ለሰማይ ወፎች ሁሉ፣ በምድር ላይ ለሚንቀሳቀሱ ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ማንኛውም ለምለም ተክል ምግብ እንዲሆናቸው ሰጥቻለሁ” እንዳለውም ሆነ።
☐ 31. እግዚአብሔርም (ኤሎሂም) ያደረገውን ሁሉ አየ፤ እነሆም፣ እጅግ መልካም ነበረ። መሸ፤ ነጋም፤ ስድስተኛ ቀን።
 
  
  Chap.