Chap.   
☐ 1. “በዚያ ዘመን” ይላል እግዚአብሔር፤ “ለእስራኤል ነገድ ሁሉ አምላካቸው እሆናለሁ፤ እነርሱም ሕዝቤ ይሆናሉ።”
☐ 2. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ከሰይፍ የተረፈው ሕዝብ፣ በምድረ በዳ ሞገስን ያገኛል፤ እኔም ለእስራኤል ዕረፍት ለመስጠት እመጣለሁ።”
☐ 3. እግዚአብሔር ከሩቅ[55] ተገለጠልን፤ እንዲህም አለን፤ “በዘላለማዊ ፍቅር ወድጄሻለሁ፤ ስለዚህም በርኅራኄ ሳብሁሽ።
[55] ወይም እግዚአብሔር ከጥንት / ከቀድሞ ተገለጠልን☐ 4. የእስራኤል ድንግል ሆይ፤ እንደ ገና አንጽሻለሁ፤ አንቺም ትታነጪያለሽ፤ ከበሮችሽንም እንደ ገና አንሥተሽ፣ ከሚፈነጥዙት ጋር ትፈነድቂያለሽ።
☐ 5. እንደ ገናም በሰማርያ ኰረብቶች ላይ፣ ወይን ትተክያለሽ፤ አትክልተኞች ይተክሏቸዋል፤ በፍሬውም ደስ ይላቸዋል።
☐ 6. ጠባቂዎች፣ በኤፍሬም ኰረብቶች ላይ፣ ‘ኑ፤ ወደ ጽዮን፣ ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር እንውጣ!’ ብለው የሚጮኹበት ቀን ይመጣል።
☐ 7. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ስለ ያዕቆብ በደስታ ዘምሩ፤ ስለ ሕዝቦች አለቃ እልል በሉ፤ ምስጋናችሁን አሰሙ፤ ‘እግዚአብሔር ሆይ፤ የእስራኤልን ቅሬታ፣ ሕዝብህን አድን’ በሉ።
☐ 8. እነሆ፤ ከሰሜን ምድር አመጣቸዋለሁ፤ ከምድርም ዳርቻ እሰበስባቸዋለሁ፤ በመካከላቸውም ዕውሮችና አንካሶች፣ ነፍሰ ጡርና በምጥ ላይ ያሉ ሴቶች ይገኛሉ፤ ታላቅም ሕዝብ ሆነው ይመለሳሉ።
☐ 9. እያለቀሱ ይመጣሉ፤ እያጽናናሁ አመጣቸዋለሁ፤ እኔ ለእስራኤል አባት ነኝና፣ ኤፍሬም በኵር ልጄ ነውና፣ በውሃ ምንጭ ዳር፣ በማይሰናከሉበት ቀና መንገድ እመራቸዋለሁ።
☐ 10. “ሕዝቦች ሆይ፤ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ ሩቅ ባሉ የባሕር ጠረፎችም፣ ‘እስራኤልን የበተነ እርሱ ይሰበስበዋል፤ መንጋውንም እንደ እረኛ ይጠብቃል’ ብላችሁ ዐውጁ።
☐ 11. እግዚአብሔር ያዕቆብን ይዋጀዋልና፤ ከእርሱም ከሚበረቱት እጅ ይታደገዋልና።
☐ 12. መጥተውም በጽዮን ተራራ ላይ በደስታ ይዘምራሉ፤ በእግዚአብሔርም ልግስና፣ በእህሉ፣ በወይን ጭማቂውና በዘይቱ፣ በፍየልና በበግ ጠቦት፣ በወይፈንና በጊደር ደስ ይሰኛሉ፤ ውሃ እንደማይቋረጥባት የአትክልት ስፍራ ይሆናሉ፤ ከእንግዲህም አያዝኑም።
☐ 13. ኰረዶች ይዘፍናሉ፤ ደስም ይላቸዋል፤ ጐረምሶችና ሽማግሌዎችም ይፈነጥዛሉ፤ ልቅሶአቸውን ወደ ደስታ እለውጣለሁ፤ ከሐዘናቸውም አጽናናቸዋለሁ፤ ደስታንም እሰጣቸዋለሁ።
☐ 14. ካህናቱን አትረፍርፌ እባርካለሁ፤ ሕዝቤም በልግስናዬ ይጠግባል፤” ይላል እግዚአብሔር።
☐ 15. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ዋይታና መራራ ልቅሶ፣ ከራማ ተሰማ፤ ልጆቿ የሉምና፣ ራሔል አለቀሰች፤ መጽናናትም እንቢ አለች።”
☐ 16. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ድምፅሽን ከልቅሶ፣ ዐይኖችሽንም ከእንባ ከልክይ፤ ድካምሽ ያለ ዋጋ አይቀርምና፤” ይላል እግዚአብሔር። “ከጠላት ምድር ይመለሳሉ፤
☐ 17. ስለዚህ ወደ ፊት ተስፋ አለሽ” ይላል እግዚአብሔር። “ልጆችሽ ወደ ገዛ ምድራቸው ይመለሳሉ።
☐ 18. “የኤፍሬምን የሲቃ እንጒርጒሮ በእርግጥ ሰምቻለሁ፤ ‘እንዳልተገራ ወይፈን ቀጣኸኝ፤ እኔም ተቀጣሁ። አንተ እግዚአብሔር አምላኬ ነህና፣ መልሰኝ፤ እኔም እመለሳለሁ።
☐ 19. ከአንተ ከራቅሁ በኋላ፣ ተመልሼ ተጸጸትሁ፤ ባስተዋልሁም ጊዜ፣ ጭኔን መታሁ፣ የወጣትነት ውርደቴን ተሸክሜአለሁና፣ ዐፈርሁ፤ ቀለልሁም።’
☐ 20. ኤፍሬም የምወደው፣ ደስም የምሰኝበት ልጄ አይደለምን? ብዙ ጊዜ ተቃውሜው ብናገርም፣ መልሼ ስለ እርሱ አስባለሁ፤ አንጀቴ ይላወሳል፤ በታላቅ ርኅራኄም እራራለታለሁ፤” ይላል እግዚአብሔር።
☐ 21. “የጐዳና ምልክት አቁሚ፤ መንገድ አመልካች ትከዪ፤ የምትሄጂበትን መንገድ፣ አውራ ጐዳናውን አስተውዪ፤ ድንግሊቱ እስራኤል ሆይ፤ ተመለሺ፤ ወደ ከተሞችሽም ግቢ።
☐ 22. አንቺ ከዳተኛ ልጅ ሆይ፤ እስከ መቼ ትቅበዘበዣለሽ? እግዚአብሔር በምድር ላይ አዲስ ነገር ይፈጥራል፤ ሴት በወንድ ላይ ከበባ ታደርጋለች።[56]
[56] ወይም መፈለግ ትጀምራለች ወይም መጠበቅ ትጀምራለች☐ 23. የእስራኤል አምላክ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ምርኮአቸውን በመለስሁላቸው ጊዜ፣[57] እነርሱ በይሁዳ ምድርና በከተሞቿ፣ ‘አንተ የጽድቅ ማደሪያ ቅዱስ ተራራ ሆይ፤ እግዚአብሔር ይባርክህ!’ የሚል አነጋገር እንደ ገና ይጠቀማሉ።
[57] ወይም ዕድል ፈንታቸውን በመለስኩላቸው☐ 24. ገበሬዎችና ዘላን ከብት አርቢዎች በይሁዳና በከተሞቿ በአንድነት ይኖራሉ።
☐ 25. የዛለችውን ነፍስ ዐድሳለሁ፤ የደከመችውንም አበረታለሁ።”
☐ 26. በዚህ ጊዜ ከእንቅልፌ ነቅቼ ዙሪያዬን ተመለከትሁ፤ እንቅልፌም ጣፋጭ ሆኖልኝ ነበር።
☐ 27. “እነሆ፤ የእስራኤልን ቤትና የይሁዳን ቤት” ይላል እግዚአብሔር፤ “በሰውና በእንስሳት ዘር የምሞላበት ጊዜ ይመጣል፤
☐ 28. ልነቅላቸውና ላፈርሳቸው፣ ልገለብጣቸውና ላጠፋቸው፣ መከራም ላመጣባቸው እንደ ተጋሁ ሁሉ፣ ላንጻቸውና ልተክላቸው ደግሞ እተጋለሁ” ይላል እግዚአብሔር።
☐ 29. “በዚያ ዘመን ሰዎች ዳግመኛ፣ ‘አባቶች በበሉት ጐምዛዛ የወይን ፍሬ፣ የልጆች ጥርስ ጠረሰ’ የሚለውን ምሳሌ አይናገሩም።
☐ 30. ነገር ግን፣ እያንዳንዱ በገዛ ኀጢአቱ ይሞታል፤ ጐምዛዛ የወይን ፍሬ የሚበላ ሁሉ የራሱን ጥርስ ይጠርሳል።
☐ 31. “ከእስራኤል ቤትና፣ ከይሁዳ ቤት ጋር” ይላል እግዚአብሔር፤ “አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት፣ ጊዜ ይመጣል።
☐ 32. ከግብፅ አወጣቸው ዘንድ፣ እጃቸውን ይዤ በመራኋቸው ጊዜ፣ ከአባቶቻቸው ጋር እንደ ገባሁት ኪዳን አይደለም፤[58] የእነርሱ ባል ሆኜ ሳለሁ፣ ቃል ኪዳኔን አፍርሰዋልና።”[59] ይላል እግዚአብሔር።
[58] የዕብራይስጡ፣ የሰብዓ ሊቃናትና የሱርሰት ትርጒሞች እኔም ዘወር አልሁባቸው ይላሉ።    [59] ወይም የእነርሱ ጌታ☐ 33. “ነገር ግን ከዚያ ጊዜ በኋላ፣ ከእስራኤል ቤት ጋር የምገባው ኪዳን ይህ ነው” ይላል እግዚአብሔር፤ “ሕጌን በልቡናቸው አኖራለሁ፤ በልባቸውም እጽፈዋለሁ። እኔ አምላክ እሆናቸዋለሁ፤ እነርሱም ሕዝቤ ይሆናሉ።
☐ 34. ከእንግዲህ ማንም ሰው ባልንጀራውን፣ ወይም ወንድሙን፣ ‘እግዚአብሔርን ዕወቅ’ ብሎ አያስተምርም፤ ከትንሹ ጀምሮ እስከ ትልቁ፣ ሁሉም እኔን ያውቁኛልና፤” ይላል እግዚአብሔር። “በደላቸውን ይቅር እላለሁ፤ ኀጢአታቸውንም መልሼ አላስብም።”
☐ 35. በቀን እንድታበራ፣ ፀሓይን የመደበ፣ በሌሊት እንዲያበሩ፣ ጨረቃንና ከዋክብትን ያዘዛቸው፣ የሞገዱ ድምፅ እንዲተምም፣ ባሕሩን የሚያናውጥ፣ ስሙ የሰራዊት ጌታ የሆነ፣ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤
☐ 36. “ይህ ሥርዐት በፊቴ ከተሻረ፣” ይላል እግዚአብሔር፤ “በዚያ ጊዜ የእስራኤልም ዘር በፊቴ፣ መንግሥት መሆኑ ለዘላለም ይቀራል።”
☐ 37. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “በላይ ያሉትን ሰማያትን መለካት፣ በታችም ያሉትን የምድር መሠረቶች መመርመር ከተቻለ፣ በዚያ ጊዜ የእስራኤልን ዘር ሁሉ፣ ስላደረጉት ነገር ሁሉ እጥላቸዋለሁ፤” ይላል እግዚአብሔር።
☐ 38. “እነሆ ከሐናንኤል ግንብ ጀምሮ እስከ ማእዘኑ በር ድረስ” ይላል እግዚአብሔር፤ “ይህች ከተማ ለእግዚአብሔር የምትሠራበት ጊዜ ይመጣል፤
☐ 39. መለኪያ ገመዱም ከዚያ ጀምሮ በቀጥታ ወደ ጋሬብ ኰረብታ፣ አልፎም ወደ ጎዓ ይዘረጋል።
☐ 40. ሬሳና ዐመድ የሚጣልበት ሸለቆ በሙሉ፣ በምሥራቅ በኩል የቄድሮንን ሸለቆ ይዞ እስከ ፈረስ በር የሚደርሰው ደልዳላ ቦታ ሁሉ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ይሆናል፤ ከእንግዲህም ከተማይቱ አትነቀልም፤ አትፈርስምም።”
 
  
  Chap.